Saturday, March 30, 2013


ኢትዮጵያ የገጠማት ከፍተኛ የዉጭ ምንዛሬ እጥረት ወያኔና ነጋዴዉን ማጨቃጨቁ ተነገረ

ካለፈዉ አመት አጋማሽ ጀምሮ ኢትዮጵያ ዉስጥ በከፍተኛ ፍጥነት እያሽቆለቆለ  የመጣዉ የዉጭ ምንዛሬ ክምችት በፈጠረዉ ችግር የተነሳ የንግዱ ህብረተሰብና የወያኔ አገዛዝ ታይቶ የማይታወቅ ጭቅጭቅ ዉስጥ መግባታቸዉን አንድ በቅርቡ ንብረታቸዉን ሽጠዉ ወደ አዉሮፓ የመጡ ኢትዮጵአዊ ነጋዴ ተናገሩ። እኚህ ላለፉት 17 አመታት በዉጭ ንግድ ስራ  ላይ ተሰማርተዉ የነበሩ አቶ አሀዱ ወሰንየለህ የተባሉ ነጋዴ እንደተናገሩት በአገሪቱ ውስጥ የተፈጠረውን ከፍተኛ የዶላር እጥረት ተከትሎ ነጋዴዎች ላለፉት 8 ወራት  እቃዎችን ወደ አገር ዉስጥ ማስገባት አልቻሉም፤ አንደ አቶ አሀዱ አባባል በአሁኑ ወቅት ከዉጭ አገር የሚገቡ ዕቃዎችን የሚያስገባዉ የወያኔ አገዛዝ ብቻ ሲሆን አገዛዙ የሚያስገባዉ ደግሞ  የግንባታ እቃዎችን ብቻ በመሆኑ የዉጭ ምንዛሬዉ እጥረት የገበያ መዛባት፤ የዕቃዎች እጥረትና የዋጋ ግሽበት እንዲከስት አድርጓል ብለዋል።
ግራ የተጋባዉ የወያኔ አገዛዝ ሰሞኑን ለነጋዴዎች ባስተላለፈው መመሪያ መሰረት በዉጭ ንግድ ዘርፍ ዉስጥ የተሰማራ ማንኛዉም ነጋዴ የውጭ ምንዛሬ ማግኘት እንደሚችል ግልጽ ያደረገ ቢሆንም በአዲሱ መመሪያ መሰረት የውጭ ምንዛሬ የሚጠይቁ ነጋዴዎች በቅድሚያ የጠየቁትን ያክል ገንዘብ በብር ለባንኮች የማቅረብ ግዴታ አለባቸው። ለምሳሌ 100 ሺ ዶላር የሚጠይቅ ነጋዴ ቢያንስ አንድ ሚሊዮን አምስት መቶ ሺ ብር በቅድሚያ ለባንኮች የማቅረብ ግዴታ አለበት። ይህንን አዲስ አሰራር የንግዱ ህብረተሰብ በፍጹም እንዳልተቀበለዉ የሚታወቅ ሲሆን በነጋዴውና በወያኔ አገዛዝ መካከል ዉዝግብ የፈጠረዉም ይሄዉ አዲሱ መመሪያ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል። ኢትዮጵያ ዉስጥ የመለስ ዜናዊን ሞት ተከትሎ ብዛት ያላቸዉ ሰዎች ገንዘብ ማሸሽ በመጀመራቸዉ ከፍተኛ የዉጭ ምንዛሬ እጥረት መከሰቱ የሚታወቅ ሲሆን ባለፈዉ መስከረም ወር ኃ/ማሪያም ደሳለኝ የጠ/ሚኒስትርነቱን ቦታ እንደተረከበ ኢትዮጵያ ዉስጥ ምንም አይነት የዉጭ ምንዛሪ እጥረት አለመኖሩን መናገሩ የሚታወስ ነዉ።
ኢትዮጵያ ዉስጥ የተፈጠረዉን የዉጭ ምንዛሬ እጥረት አስመልክቶ አስተያየታቸዉን እንዲሰጡን የጠየቅነቸዉ አንድ የአኮኖሚክስ ምሁር የወያኔ አገዛዝ የገንዘብ እጥረት ቢያጋጥመው አይገርምም፣ ከመለስ ሞት በኋላ የወጡ ወጪዎችን እንኳን ብናይ፣ ይህች ደሀ አገር  ያለአቅሟ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ  አውጥታለች ካሉ በኋላ፤ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀብር ማስፈጸሚያ ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ፤ የብሄር ብሄረሰቦች በአል ለማክበር ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ የመከላከያ ቀንን ለማክበር ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጓል።  አሁን በቅርቡ ደግሞ የወያኔ ኢህአዴግን ጉባኤ ለማካሄድና  የአባይን ግድብ ሁለተኛ አመት ለማክበር ከፍተኛ ገንዘብ ከመንግስት ካዝና ወጪ ሆኗል ። እንግዲህ እንደዚህ አይነት ከፍተኛ መጠን ያለዉ ገንዝብ ከልማት ጋር ባልተያያዘ መንገድ እየወጣ አገሪቱ የገንዘብ እጥረት ገጠማት ቢባል የሚገርም ሊሆን አይገባም  ብለዋል።
  • facebook

No comments:

Post a Comment