Wednesday, December 3, 2014
ምን አይነት ሰላማዊ ሰልፍ?
በተክሉ አባተ (teklu.abate@gmail.com)
ለመጀመሪያ ጊዜ በሰላማዊ ሰልፍ የተሳተፍኩት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ 6 ኪሎ ግቢ ተማሪ እያለሁ ነበር:: በአራት ዓመት
የትምህርት ቆይታዬ በርከት ያሉ ሰልፎች ተካሂደዋል:: አንዳንዴ የምግብ ጥራት ማሽቆልቆሉን በመቃወም ሌላ ጊዜ ነጻነትን
ፍትህንና ዴሞክራሲን እንዲሁም የመሬት ክፍፍልን በመቃወም:: ምግብን በተመለከተ የተቀናጁ ሰልፎች አጀማመራቸው
ምግብ-ነክ ይሁን እንጅ መደምደሚያቸው ፖለቲካ ነበር:: ድንገት ከሰልፉ መካከል አንዱ ተነስቶ "ፍትህና መብት ይከበር"
ካለ ተሜ ወዲያው ተቀብሎ ያስተጋባዋል:: አንዳንዶች ደግሞ በራሳቸው ተነሳሽነት ቀድሞ የተዘጋጀ የጽሁፍ መፈክር ብቅ
ያደርጋሉ:: በአቅራቢያቸው ያለ ተሜ እያነበበ ያስተጋባዋል:: ሌላው ይቀበለዋል:: የአንገት ስር እስኪወደር ድረስ ይፎከራል::
ስሜት እየጋለ ይሄዳል:: የተሰላፊው ቁጥር የሚጨምረው ሰልፉ ከተጀመረ ከበርካታ ደቂቃዎች በኋላ ነው:: መጀመሪያ
ላይ ፈራ ተባ እያሉ ከዳር ሆነው የሚመለከቱ ይበዛሉ.: በኋላ ድንገት ሰልፉን የሚቀላቀሉ ይበዙና ተሰላፊው ዋናውን በር
የሚወጣው በሦስትና አራት ረድፍ ባለው ረጅም መስመር ነው::
የሚገርመው ሰልፉ ሰላማዊ ተብሎ ቢጀመርም ሰይፋዊ ሆኖ ይጠቃለላል:: ካድሬ ሰላይ ፖሊስና ወታደር ሙያቸውን
የሚያስመሰክሩበት ልዩ አጋጣሚ እስኪመስል ድረስ አካባቢውን ያጥለቀልቁታል:: ከጥቂት ማስፈራራት በኋላ ወደ ርምጃ
ይሸጋገራሉ:: ተሜም እድሉን የሚለካበት ጊዜ ይገጥመዋል:: ግርግርና ዱላ በጥበቃ አካላት ይጀመራል:: ጥጋቸውን ይዘው
በሚጠባበቁ አይፋ በሚባሉ ወታደራዊ መኪናዎች ተሜ ወደ ማሰቃያ ጣቢያዎች ይወሰዳል:: በደንብ የሚደበደቡ: የሚታሰሩ:
ከትምህርታቸው የሚባረሩ: ማስጠንቀቂያ የሚሰጣቸው ብዙ ናቸው:: ጀርባቸው እስኪላጥ እግራቸው እስኪጠቁር በፖሊስ
የሚሰቃዩ ሞልተዋል:: በተለይ ሸጎሌ ተብሎ ከሚጠራው መጠርነፊያ ጣቢያ የተወሰዱት ያጋጠማቸው ስቃይ 'ታሪካዊ' ነበር::
በባዶ እግራቸው እንደጦር በቆመ አሸዋ ላይ ያሴዷቸው ነበር:: በካድሬዎች ወከባ የተነሳ ትምህርት ያቋረጥንባቸው ጊዜያትም
ነበሩ::
የበለጠ የሚገርመው ደግሞ ለቀናት ከሚዘልቀው አካላዊ ስቃይ ይልቅ ተማሪዎች የሚደርስባቸው ሥነ-ልቦናዊ ጥቃት
ነበር::ተማሪዎች ከእስርና ከስቃይ ለመውጣት ከፈለጉ መንግስትን ይቅርታ እንዲጠይቁ ይገደዳሉ:: ከዚያም በማናቸውም
ተመሳሳይ ሰልፎች ወይም ዝግጆቶች ላይ ወደፊት እንደማይሳተፉ በሚገልጠው ሰነድ ላይ እንዲፈርሙ ይደረጋሉ:: በመሆኑም
ከእስራታቸው በኋላ ትንፍሽ እንኳን የማይሉ እየተበራከቱ መጥተው ነበር:: እስካሁንም ድረስ ያንን የገቡትን 'ቃል
ኪዳን' ታሳቢ በማድረግ በመሳቀቅ የሚኖሩ አሉ::
ውጤታቸው ምንም ይሁን ምን የተደረጉ ሰልፎች መደረግ የነበረባቸው ናቸው ብዬ አምናለሁ:: ውጤት ያመጡ ሰልፎች
ነበሩ:: እነወይዘሮ ገነት ዘውዴ እና እነ ዶክተር ዱሪ ላባቸው እስኪመጣ ድረስ በተሜ ተፋጠዋል:: ቀላል የማይባሉ
ለውጦችም ወዲያውኑ ተደርገዋል:: እነዚያ ሰልፎች የተማሪን ህይወት ያማከሉ ቢመስሉም (አንዳንድ የአዲስ አበባ ኗሪዎችተሜ ለዳቦ ጥራት እንጅ ለሃገሩ እድገት አይሰለፍም እያሉ ቢሳለቁም) ከብሄራዊ የዜግነት ግዴታዎችና መብቶች ጋር የተያያዙ
ናቸው:: ነጻነት ፍትህ እኩልነት የተጠየቀባቸው ሰልፎች ነበሩና::
የሰልፍ ሁሉ መጀመሪያ
ከላይ ያለውን ታሪክ ያነሳሁት እንደመግቢያ እንዲያገለግለኝ ነው:: ዋናው ነጥቤ በአሁኑ ጊዜም ኢትዮጵያ ውስጥ የሰላማዊ
ሰልፍን አስፈላጊነት ለማመላከት ነው:: የዜግነት መብት እስካልተከበረ ድረስ ሰልፍ ይካሄዳል:: ለመብትና ለአገር ክብር
የሚደረግ ሰልፍ ሰው የመሆን አንዱ መገለጫ ነው:: ሰልፉ ግን መጀመር ያለበት ከግል ህይወት ነው:: በማይጠቅሙ ሃሳቦች
የተሞላ አእምሮ ያለው ሰው በራሱ ላይ ሰልፍ መውጣት አለበት:: መብቱ በጓደኛው ወይም በሥራ ባልደረባው የሚጣስበት
ካለ በዚያ ላይ ሰልፍ መውጣት አለበት:: አባል የሆነበት ድርጅት መብቱን የሚጥስበት ከሆነ ሰልፍ መውጣት አለበት:: ሰልፍ
መውጣትም በአካል ወደአደባባይ መንጎድን ብቻ አይመለከትም:: ፍርሃትንና ይሉኝታን አስወግዶ ሃሰተኞች ወይም መብት
እረጋጮች የሚሰሩትን ግፍ ፊትለፊት መናገርንም ያጠቃልላል:: በአደባባይ ሰልፍ ተገኝቶ በጓዳ መብቱንና ጥቅሙን የሚያስነካ
ሰው ራሱን ያታልላል:: በውስጥም በውጭም በአካልም በሥነ-ልቦናም በግልም በቡድንም በደልን መቃወም ማጋለጥም
ያስፈልጋል:: "መብቴ ተጣሰ" ብሎ ሰልፍ የሚወጣ የሌላውን ሰው መብት መጠበቅም ሊኖርበት ነው:: እያንዳንዳችን
ለራሳችን መብት ሳናቋርጥ ሰልፍ መውጣት አለብን:: ይህ ከሆነ ነው የቡድን ሰልፎች የሚያምርባቸውና ውጤታማ
የሚሆኑት:: ብዙ ሰዎች አብዝተው የሚጨነቁት ግን በቡድን ስለሚደረግ ሰልፍ ነውና ለጊዜው እሱን እንመልከት::
ውጤታማ ሰልፍ
በአጠቃላይ ሲታይ የትም ቦታ በማናቸውም ጊዜ የሚደረጉ ህግን መሠረት ያደረጉ የቡድን ሰላማዊ ሰልፎች ሁሉ ልዩ ባህርይ
አላቸው:: ዳሩ ግን አንድ ሰልፍ ግልጽ ዓላማዎችና የአፈጻጸም ስልቶች ሊኖሩት ይገባል:: ይህ ደግሞ በጊዜና በቦታ ሊወሰን
ይችላል.: ያም ሆኖ አንድን ሰልፍ ውጤታማ ነው ብሎ ለመፈረጅ በርካታ መለኪያዎችን ማሟላት ይኖርበታል:: ለእኔ የተሳካ
ሰልፍ ማለት ቀጥለው የተዘረዘሩትን የአጭር የመካከለኛና የረጅም ጊዜያት አብዛኞችን መስፈርቶ ች ያሟላል::
ሰልፉን ተከትሎ ተሰላፊዎች በራስ የመተማመንና የእርካታ ስሜት ማግኘት አለባቸው
ተሰላፊዎች በቋሚነት የራሳቸውንና የወገናቸውን መብቶች ለማስጠበቅ ጽኑ አቋም ይይዛሉ
ሰልፍ ህግን በማያከብረው በመንግስት ላይ ስጋትና ፍርሃትን ማስፈን አለበት
መንግስት ለጊዜው በይፋ ለውጦችን ለማድረግ ቃል ባይገባም ወደዚያው የሚያደርሱ እንቅስቃሴዎችን እንዲያደርግ
ማስገደድ አለበት
መንግስት ተረጋግቶ ጭቆናውን እንዳይቀጥል ያደርገዋል
የመንግስትን ጨቋኝነት የሌሎች ሃገራት መሪዎችና ተቋማት በደንብ እንዲያውቁት ያደርጋል
አንዱ ሰልፍ ሌላ ሰልፍ ይወልዳል
በሰልፉ ምክንያት የሚታሰር የሚደበደብ የሚሰደድ ወዘተ ካለ ስለእሱም ፍትህ ይጠይቃል ሌላ ሰልፍ በተሻለ ሁኔታ
ይደረጋል መንግስት በሚያደርጋቸው ጥቂት የማስታገሻ ማሻሻያዎች አይታለልም
በመጨረሻም የሚፈለገው ለውጥ በመጠንና በዓይነት ይገኛል
የውጤታማ ሰልፍ መገለጫ ባህርያት
ከላይ የተዘረዘሩትን እንዲሁም ሌሎችን ውጤቶች ለማሳካት አንድ ሰላማዊ ሰልፍ ማሟላት ያለበት ባህርያት ይኖራሉ::
ጥቂቶችን እንዲህ ዘርዝያለሁ::
በደንብ የተደራጀና የተመራ ሰልፍ የተሰላፊውን ቀልብ ከመሳብ በተጨማሪ ያልተሰለፉ ሰዎችም ወደፊት እንዲሰለፉ
ይጋብዛል
ለረጅም ጊዜ ወይም በተከታታይ የሚደረግ ሰልፍ እጅግ አመርቂ ውጤት ያመጣል
ሰልፍ በሚደረጉ መጥፎ ሥራዎች ላይ ያለን ተቃውሞ ለማሰማት ብቻ ሳይሆን ለውጥ እንዲደረግ
የሚያስገድድ መሆን አለበት
ሰልፍ መንግስት መመለስ ያለበት ግልጽ ጥያቄዎችን ማቅረብ አለበት
እንደ ጉዳዮች ትልቅነትና አሳሳቢነት እየታየ መንግስት መልስ የሚሰጥበት ጊዜም መገለጽ አለበት
በተሰጠው ጊዜ መንግስት አጥጋቢ መልስ ካልሰጠ በአይነቱና በመጠኑ ልዩ የሆነ የተቀነባበረ ሰልፍና ህዝባዊ
ተቃውሞ እንደሚደረግ ማሳወቅ አለበት
ሰልፍ አስተባባሪዎች ሊታሰሩ ወይም ሊሰው ስለሚችሉ በርካታ መሪዎችን ማዘጋጀት ያስፈልጋል
ህዝቡ መብቱን በሚገባ እንዲያውቅና ትግሉን በቀጣይነት እንዲመራ ማድረግ ወሳኝነት አለው
ህዝቡ ኃይልንና ስሜትን ተቆጣጥሮ ከሰልፉ ዓላማ ላይ ትኩረትን ማድረግ እንዳለበት መነገር አለበት
ህዝቡ በአቋሙ ከጸና ጨቋኝ መሪዎች እንደሚሸነፉ ማስተማርና ሥልጣን የህዝብ እንደሆነ ማሳሰብ ያስፈልጋል
ፖሊስና ወታደር በሚመጣበት ጊዜ ከመሮጥ ይልቅ ሁሉም ተረጋግቶ ባለበት እንዲጸና ማድረግ ያስፈልጋል
ማጠቃለያ
የኢትዮጵያ ህዝብ የግልም ሆነ የቡድን መብቱ ተረግጧል:: ኑሮ ከአቅሙ በላይ ሆኗል:: ይህ አላንስ ብሎ ያሰበውን
እንዳይናገር አንደበቱ ተዘግቷል:: በተጨማሪም መንግስት አንዱ ህዝብ በሌላው ላይ እንዲነሳ የቻለውን ሁሉ እያደረገ ነው::
በመሆኑም እውነተኛ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ አማራጭ የሌለው የመኖርና ያለመኖር ጉዳይ ሆኗል.: አገር ቤት ሆነው
የሚታገሉት ዘጠኝ የፖለቲካ ፓርቲዎች የአንድነት መድረክ በመፍጠር ሰላማዊ ሰልፍ ከህዳር 27/2007 ዓ.ም እስከ ህዳር
28/2007 ዓ/ም ለማድረግ በዝግጅት ላይ ይገኛሉ:: ይህ በዓይነቱ የተለዬ ሰልፍ በሁሉም ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያዊ
ሊደገፍና ሊበረታታ ይገባል:: በአካል በሞራል በሃሳብና በገንዘብ መደገፍ ይኖርብናል:: የሰልፉ አስተባባሪዎችም እጅግ ጥበብ የተሞላበት እቅድ ነድፈው ህዝቡን ደረጃ በደረጃ መምራት አለባቸው:: መንግስት
ሊያሟላቸው የሚገቡ ጉዳዮች በቁጥር ተለይተው እስከነ ጊዜ ገደባቸው መቅረብ አለባቸው:: ጥያቄዎች የማይመለሱ ከሆነ
ቀጣይነት ወዳለው ህዝባዊ ተቃውሞ ማሸጋገር ያስፈልጋል:: መስቀል አደባባይን እንደ ዋና ቢሮ አድርጎ በመላ ኢትዮጵያ
ተመሳሳይ እንቅስቃሴ እንዲካሄድ ማድረግ ወሳኝነት አለው:: ሰልፉ በመጠንና በቦታ ባደገ ቁጥር የመንግስት ጫና እየላላ
ይሄዳል:: በመጨረሻም የህዝብ መብት ተከብሮ ሥልጣን ለህዝብ ይሆናል:: ከዚያም ኢትዮጵያውያን ዜግነታቸውን
እያጣጣሙ ሃገራቸውን እንደገና በኅብረት ይገነቧታል:: አላስፈላጊው ስደትና ስቃይ ታሪክ ሆኖ ይቀራል::
Subscribe to:
Post Comments (Atom)
No comments:
Post a Comment